
How Do Christians Fit Into the Two-Party System? They Don’t
The historical Christian positions on social issues don’t match up with contemporary political alignments.
[the_ad_group id=”107″]
መጋቢ መስፍን ሙሉጌታ በኮልፌ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን በመጋቢነት ያገለግላሉ። ከዚህ በተጨማሪ፣ ዘወትር ዓርብ ቤተ ክርስቲያኒቱ በምታዘጋጀው “የፈውስና ነጻ የማውጣት” መርሓ ግብር ላይ ላለፉት በርካታ ዓመታት አገልግሎት ሲሰጡ ቆይተዋል። በዚህ ዘመን በፈውስ ስጦታ ቤተ ክርስቲያንን ያገልግላሉ ከሚባሉት አገልጋዮች መካከል የመጋቢ መስፍን ስም ቀድሞ ይነሣል። ሕንጸት ስለ መንፈስ ቅዱስ፣ ስለ ስጦታዎቹ እና አጠቃቀሙ እንዲሁም ከዚሁ ጋር ተያይዘው ስለሚነሡ ጉዳዮች ከመጋቢ መስፍን ሙሉጌታ ጋር ያደረገው ቆይታ እንደሚከተለው ቀርቧል።
መጋቢ መስፍን:- በእኔ አተያይ አሁን ያለው መደናበርና ግራ መጋባት ዝም ብሎ የመጣ አይመስለኝም። በምድራችን ታላቅ ስደት በነበረበትና ቅዱሳን በኅቡዕ በመደራጀት ጌታን በሚያመልኩበት በዚያ የኮምኒዝም ዘመን መንፈስ ቅዱስ ብዙ ድንቅና ታምራት ሲሠራ አይተናል። በዚህ አገልግሎት ብዙዎች ሲጽናኑና ሲፈወሱ፣ በጨለማ ውስጥ የነበሩ የወንጌል ብርሃን በርቶላቸው ለሌሎች መዳን ምክንያት ሲሆኑ የማየት ዕድል አጋጥሞናል። የሚገርምህ በዚያ ዘመን የአማኙ ትኩረት የተሰቀለው፣ የሞተው፣ ከሞት የተነሣው፣ በአብ ቀኝ ባለውና ዳግመኛ ተመልሶ በሚመጣው በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ነበር። ማንም ሆን ብሎ ድንቅና ታምራትን በዚህ ዘመን እንደሚደረገው ሲያሳድድ አትመለከትም። ʻታድያ አሁን ያለው ውዥንብርና ግራ መጋባት በጸጋ ስጦታዎቹ ላይ እንዴት ሊታይ ቻለ?ʼ ላልከኝ የአብዛኛው ቅዱሳን ዐይን ከመስቀሉ ላይ ተነሥቶ ድንቅና ታምራት ላይ በማተኮሩ፣ አገልጋዮቹም የተሰጣቸውን የጸጋ ስጦታ ለወንጌል ማስፋፊያና ለቅዱሳን መታነጽ ከማድረግ ይልቅ የራሳቸውን ስም ማስጠሪያና ኑሯቸውን መደጎምያ ስላደረጉት፣ ዐይን ያወጣ ስሕተት ሲሠሩ ታስተውላለህ። ከዚህም የተነሣ እውነተኛው የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ በሐሰተኞች እየተሸፈነ በመምጣቱ መደናበሩ የመጣ ይመስለኛል። እንደዛም ሆኖ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ሁሌም ቅሬታዎች እንዳልጠፉ ሁሉ በእውነትና በተለወጠ ማንነት ጌታን የሚያመልኩ ምእመናንና አገልጋዮች ዛሬም አሉ ብዬ አጽንዖት መስጠት እፈልጋለሁ.።
መጋቢ መስፍን፡- እንደነዚህ ዐይነት ሰዎች እንደሚነሡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ስለተናገረ ዛሬ መኖራቸው እምብዛም አይደንቀኝም። ጌታ ኢየሱስ በተለምዶ የተራራው ስብከት በምንለው በማቴዎስ ምዕ 7 ከቁጥር 20-23 ላይ “በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ ʻጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይʼ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም። በዚያ ቀን ብዙዎች ʻጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይ፤ በስምህ ትንቢት አልተናገርንምን? በስምህስ አጋንንትን አላወጣንምን? በስምህስ ብዙ ታምራት አላደረግንምን?ʼ ይሉኛል። የዚያን ጊዜም፣ ʻከቶ አላወቅኋችሁም እናንተ ዐመፀኞች ከእኔ ራቁ’ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ” በማለት አስተምሯል። እነዚህ ሰዎች እኮ የኢየሱስን ስም ጠርተው ነው ትንቢት የተናገሩት፣ አጋንንትን ያወጡት፣ ብዙ ታምራትን ያደረጉት። በጣም የሚያስደነግጠኝ ጌታ ኢየሱስ በመጨረሻው የፍርድ ወንበር ላይ ሲሆን እነዚህን ሰዎች ʻከቶ አላውቃችሁም እናንተ ዐመፀኞች ከእኔ ራቁʼ አይደለም የሚላቸው፤ ይልቁንም “ከቶ አላወቅኋችሁም” ነው የሚላቸው። ስለዚህ ትንቢት መናገር፣ አጋንንትን ማስወጣትና ታምራትን ማድረግ እውነተኛ አገልጋይ ለመባል ብቻ ሳይሆን በኢየሱስ ለመታወቅ ዋስትና አይደለም ማለት ነው። ይህ ደግሞ ምን ያህል አስደንጋጭ ነው።
ታዲያ በኢየሱስ ሳይታወቁ “በአገልግሎታቸው” የታወቁትን ሐሳውያን ምእመናን ሊለዩዋቸው የሚገባው ከፍሬያቸው ነው፤ ዛፍ ከፍሬው እንደሚታወቀው ማለት ነው። ከላይ ባነሣሁት ክፍል ላይ ጌታ ኢየሱስ “በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ” የሚያደርግ ብሏል። ቀዳሚ የሆነው የእግዚአብሔር ፈቃድ፣ ሰዎች በአንድ ልጁ አምነው የዘላለምን ሕይወት እንዲያገኙ ነው። አማኞች ኢየሱስ ክርስቶስን እየታዘዙና እያመለኩ እንዲኖሩ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው። ʻየእነዚህ ሐሳውያን ፈቃድ ታድያ ምንድን ነው?ʼ ብለን መጠየቅ ከቻልን ለንዋይና ለዚህ ዓለም ተድላ መኖር፣ የክርስቶስን ስም ማላቅ ሳይሆን የእነሱ ስም እንደ ባንዲራ ከፍ ብሎ እንዲወጣ መለከት ማስነፋት የሚወዱ ናቸው። እነዚህ ሰዎች መለያቸው የሚጠፋ ዝና፣ ክብር፣ ገንዘብን መውደድና የሥነ ምግባር ውድቀት ነው። የመንፈስ ፍሬ ሳይሆን የሥጋ ፍሬ ጎልቶ ይታይባቸዋል። እነዚህ ሰዎች ሐዋርያው እንዳለው ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች፣ በአንደበታቸው ግን ማር የሚያንጠባጥቡ የሚመስሉ ናቸው። ሆኖም ትምህርታቸው በመርዝ የተለወሰ ገዳይ ነው። ክርስቶስ ተኮር ባለመሆናቸው ምእመናን በቃሉ ብርሃን አንጥረው በመመርመር ሊለዩአቸው ይገባል እላለሁ።
መጋቢ መስፍን፡- መቼም ይህ ሁኔታ በራሱ ጤናማነት አለው ብዩ አላምንም። የኢትዮጵያ የኤሌክቲሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን አንድ ወቅት መብራትን በፈረቃ ያከፋፍል እንደ ነበር ብዙዎቻችን እናስታውሳለን ብዬ ዐስባለሁ። ʻባለ ሥልጣን መሥሪያ ቤቱ ለምን ይሄንን ሊያደርግ ቻለ?ʼ ብለን ብንጠይቅ የምናገኘው መልስ የኀይል እጥረት ስላጋጠመው ነው የሚል ይሆናል። ይሄ የዚህኛው ዓለም አሠራር ሊሆን ይችላል። ወደ መንፈሳዊው ዓለም ስንመጣ ግን መንፈስ ቅዱስ ሁሉን በሁሉ መግዛት የሚችል አምላክ ነው። መንፈስ ቅዱስ እንደ ወደደ የጸጋ ስጦታዎችን ለቤተ ክርስቲያን ይሰጣል። መንፈስ ቅዱስ አይደክምም፤ የኀይል እጥረትም አያገኘውም፤ እርሱ ሁሉን ቻይ ነውና።
ደግሞም መንፈስ ቅዱስ እንደሚገባ ለመሥራት የሰዎችን ፈቃድ ይፈልጋል። ሰይጣን ነው የሰዎችን ፈቃድ ሳይጠብቅ በማስገደድ ማድረግ የሚፈልገውን የሚያደርግ። ስለሆነም ቤተ ክርስቲያን የተሰጣትን የጸጋ ስጦታዎች ጠብቃ በዘላቂነት እንድትቀጥል ካስፈለገ እንደ ኤሌክትሪክ ኀይል ባለ ሥልጣን የኀይል እጥረት ሊያጋጥማት አይገባም። ይሄ ማለት በዚህ አገልግሎት ውስጥ የሚያገለግሉ ሰዎች ዕለት ዕለት የመንፈስ ቅዱስን ኀይል መሞላት ይጠብቅባቸዋል ማለት ነው። መንፈስ ቅዱስ ፈቃዱን እንዲገልጥላቸው ዘወትር ፊቱን መፈለግ፣ መንፈስ ቅዱስን ከሚያሳዘን አስጸያፊ ልምምድ በመለየት በቅድስና ሕይወት መመላለስ ይገባል። እንደዚህ ማለት ግን ከኀጢአት የጸዳና እንከን የሌለበት ፍጹም ሕይወት መኖር ማለት ሳይሆን፣ ፈሪሓ እግዚአብሔር ያለውን ኑሮ በመኖር በንሰሓ መመላለስ ይገባል። በቤተ ክርስቲያን ወስጥ መለያየት፣ ቡድንተኛነትና ዘረኝነት መንገሥ ከጀመረ መንፈስ ቅዱስ ለመሥራት ይቸገራል። በርግጥ ይህ የሚሆነው ባሕርይው ስለማይፈቅድለት እንጂ መሥራት ስለሚያቅተው አይደለም። ስለዚህ እነዚህ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታዎች በቤተ ክርስቲያን እንዲቀጥሉ ካስፈለገ ከመንፈስ ቅዱስ ሐሳብ ጋር መስማማትና የቅድስና ሕይወት ጉልሕ ሚና ይጫወታሉ ብዬ አምናለሁ።
ሌላው እግዚአብሔር ተጠቀመብኝ የሚል ሰው ክብሩን መሻማት ሲጀምር፣ ቤተ ክርስቲያንም ለእግዚአብሔር የሚገባውን ክብር መውሰድ ስትጀምር የጸጋ ስጦታውን የሰጠ እግዚአብሔር መልሶ ሊወስደው ስለሚችል ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል ብዬ ዐስባለሁ። ለቤተ ክርስቲያንም ሆነ ለአገልጋይ የተሠመረ አንድ መሥመር አለ፤ ክብሩን አለመንካት። ይሄንን ባደረግን ጊዜ ውርደታችን እየፈጠነ ይሄዳል። የጥንት መዝሙሮችን በምናዳምጥበት ጊዜ የትኩረት አቅጣቻቸው በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ነበር። መንፈስ ቅዱስም እኮ የሚያከብረው ክርስቶስን ነው። አሁን አሁን ግን እያከበርን ያለው ክርስቶስን ሳይሆን ራሳችንን ነው። ይሄ ደግሞ ትልቅ በደል ነው። እኛ የክብሩ ተጠቃሚዎች እንጂ የክብሩ ተጋሪዎች አይደለንም፤ እግዚአብሔር አንዳች ስለ ጎደለው በእኛ አይገለገልምና።
መጋቢ መስፍን፡- መቼም በሐሰተኛና ስሕተት በሚሠራ መካከል ልዩነት አለ ብዬ ዐስባለሁ። ሆን ብለው ሐሰትን ኑሯቸው ያደረጉ አገልጋዮች የመኖራቸውን ያህል፣ የስሜትና የሥጋ ሐሳብ ተቀላቅሎባቸው የሚሳሳቱም አሉ። ይሄ አገልግሎት በራሱ ከፍተኛ ጥንቃቄን የሚጠይቅ አገልግሎት ነው። አንዳንዴ እውነተኛ ነገር ሊገለጥልህ ይችላል፤ እውነተኛውን ትርጉም ካልተረዳህ እስክትረዳው ድረስ ዝም ማለት ሲኖርብህ፣ ስሜትህ እንደነዳህ ለመተረጎም ብትሞክር መንፈስ ቅዱስ ሊያስተላልፍ የፈለገውን ሐሳብ አትረዳምና ልትስት ትችላለህ። እንደዛም ሆኖ ስሕተት የሚሠሩ ሰዎች ኀጢአት ሠርተዋልና ንሰሓ ሊገቡ ይገባል። ቤተ ክርስቲያንም ብትሆን ኀላፊነትን ስትሰጥ ከተጠያቂነት ጋር ልትሰጥ ይገባል ብዬ አምናለሁ። ሐሰትን ግን ኑሯቸው ባደረጉ ሰዎች ላይ ቤተ ክርስቲያን የሥነ ሥርዐት እርምጃ ልትወስድባቸው ይገባል። እንደዚህ የሚደረግበት ዐላማ ደግሞ ስሑት የሆነውን ለማረምና ሌሎችን ለማስተማር፣ የተሳሳተውም ከስሕተቱ ተምሮ የተሻለ ሰው እንዲሆን ለመርዳት ነው።
መጋቢ መስፍን፡- አንተ እንዳልከው እንደዚህ ዐይነቱ መረዳት ያላቸው ሰዎች ጥቂት የሚባሉ አይደለም፤ ነገር ግን ሚዛኑን የጠበቀ ዕሳቤ ነው ለማለት እቸገራለሁ። ስሕተትን ማረም እኮ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ነው። በአዲስ ኪዳን ሐዋርያው ጴጥሮስ ሲስት ሐዋርያው ጳውሎስ ፊት ለፊት ተቃውሞታል፤ ምክንያቱም የሐዋርያው ጴጥሮስ አካሄድ ሰዎች ድነትን ከሚያገኙበት ጤናማው የወንጌል አስተምህሮ ጋር የሚጣረስና ማመቻመች የተስተዋለበት ስለ ነበረ ነው። ልብ በል፤ ሐዋርያው ሲስት ዝም ተብሎ አልታለፈም፤ ፊት ለፊት ተገሰጸ እንጂ። ከዚህ የምንረዳው ልዩ የሆነ አምላክ አለን እንጂ ልዩ የሆነ የማይሳሳት ሰው የለንም። ስለሆነም እርምት የሚያደርጉ ሰዎችን በጭፍኑ በመፈረጅ የመንፈስ ቅዱስ ተቃዋሚዎች አድርጎ ማቅረብ አንድም ከእውቀት ማነስ፣ አንድም በጭፍን ለመፍረድ ካለን ልምድ የመነጨ ሊሆን ይችላል። ሌላው እርምት የሚሰጡ ሰዎችም ተቀዳሚ ዐላማቸው ሊሆን የሚገባው አገልጋዮቹን ከመቅረጽና ከማቅናት አንጻር እንጂ፣ የበለጠ ተጎድተው ከአገልግሎትና ከቅዱሳን ኅብረት እንዲጠፉ የሚያደርግ እንዳይሆን ብርቱ ጥንቃቄ ያስፈልጋል ብዬ በጽኑ አምናለሁ።
መጋቢ መስፍን፡- እንደ እውነቱ ከሆነ ይሄ ጥያቄ በተደጋጋሚ ሲነሣ እሰማለሁ፤ አግባብነት ያለው ጥያቄም ነው እላለሁ። ቀኖች ሁሉ የእግዚአብሔር ናቸው። መንፈስ ቅዱስን በጊዜና በቀን ልንገድበው አይገባም፤ ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ መቼና እንዴት ፈቃዱን በሰዎች ሕይወት ላይ መፈጸም እንዳለበት ያውቃልና። በሌላው ጎኑ መጽሐፍ ቅዱሳችን በግልጽ እንደሚያስተምረው የጸጋ ስጦታዎች ልዩ ልዩ ናቸው። ሁሉ ትንቢት የመናገር፣ ሁሉ የፈውስ፣ ሁሉ ታምራት የማድረግ ስጦታ አልተሰጣቸውም፤ ይልቁንም ለእያንዳንዱ የተለያየ የጸጋ ስጦታ ተሰጥቷል እንጂ። ታድያ እዚህ ላይ ልንገነዘብ የሚገባው ነገር ቢኖር፣ ሁሉ የመፈወስ ስጦታ ከሌላቸው፣ ሁሉ ታምራት የማድረግ ስጦታ ካልተሰጣቸው በዚህ ስጦታ የሚያገለግሉ ሰዎች ሊወስዷቸው የሚገቡ ጥንቃቄዎች አሉ።
አገልጋዮቹ ራሳቸው ሰው እንደ መሆናቸው ውስኖች ናቸው። እያንዳንዱ የታመመ በሽተኛ እንዲፈወስ፣ በእያንዳንዱ ሰው ቤት ሄዶ መጸለይ የሚወስደውን ጊዜ ከግምት ውስጥ ሊያስገቡ ይገባቸዋል። ይሄ ማለት ግን ሰው ቤት ሄዶ መጸለዩ አግባብነት የለውም እያልኩ አይደለም። ሌላው በየቀኑ የፈውስ ፕሮግራም አለ ብለው አገልግሎቱን ቢጀምሩ ምን ያህል ማዝለቅ ይችላሉ። አገልግሎቱ በራሱ ጊዜ እንድንወስድ፣ እንድንጾም ቃሉን እንድናጠና መንፈስ ቅዱስን እንድንሰማ የሚያስገድደን አይሆንም ወይ? በአጠቃላይ ቤተ ክርስቲያን ቀንን የምትቀጥረው መንፈስ ቅዱስ በዚህ ቀን ብቻ ነው የሚሠራው ለማለት ፈልጋ ሳይሆን፣ ጥራት ያለው አገልግሎት ከመስጠት አንጻርና አገልጋዮቹም ተገቢውን የዝግጅት ጊዜ እንዲኖራቸው ከማድረግም አንጻር ጭምር ነው። አገልጋዮቹም የሥጋ ድካም ሊያጋጥማቸው እንደሚገባ ማሰብ ተገቢ ነው እላለሁ።
ሌላው አገልጋዮች ልንወስደው የሚገባ ነገር ቢኖር እኛ የመንፈስ ቅዱስን ፈቃድ አስፈጻሚዎች እንጂ አመንጪዎች አይደለንም። እኛ ሕዝብ በተሰበሰበበት መንፈስ ቅዱስ ዝም ካለ እኛም ዝም ልንል ይገባናል። እሱ ያልተናገረውን መናገር ለእኛ በደል ነው የሚሆነው፤ ሕዝቡንም አይጠቅመውም። ስለሆነም መንፈስ ቅዱስ ካልተናገረ ʻእኔ የምነግራችሁ አንዳች የለምʼ ብሎ ጉባኤውን ማሰናበት ጤናማነት ነው ብዬ አምናለሁ። እንደዚህም ስልህ ወደዚህ መረዳት መጥቶ ተግባራዊ ማድረግ ሥጋዊ የሆነ አስተሳሰብን መጨቆን ስለሚጠይቅ ቀላል ነገር ነው እያልኩህ አይደለም። መሆን ያለበት ግን ይሄና ይሄ ብቻ ነውና የግድ ልናደርገው ይገባል።
መጋቢ መስፍን፡- አማኞች የክርስቶስ ተከታዮች መሆናቸው ይቀርና ሰዎችን የሚከተሉ ከርታቶች ይሆናሉ፤ አማኞች በእውነተኛው የጸጋ ስጦታዎች ላይ ጥርጣሬ እንዲኖራቸው፣ ብሎም ‘በዚህ ዘመን ስጦታዎቹ መሥራት አቁመዋል’ ወደሚል የተሳሳተ መረዳት ውስጥ እንዲገቡ ይሆናሉ። አገልጋዮቹ የጸጋ ስጦታዎቹን ወንጌልን ለመስበክና ቅዱሳንን ለማነጽ ከማዋል ይልቅ፣ ምድራዊ ኑሯቸውን ለመለወጫነት፣ በሥነ ምግባር ውድቀት ውስጥ በመዘፈቅ ለክርስቶስ ስም መሰደቢያና ቤተ ክርስቲያን በተቃዋሚዎችዋ ፊት አንገቷን ደፍታ እንድትሄድ ሊያደርጋት ይችላል። በአጠቃላይ ሊፈጠር የሚችለውን አሉታዊ ጎን ዘርዝረህ የምትጨርሰው አይደለም፤ ይሄ ደግሞ እጅግ ልብን የሚሰብር ነው።
መጋቢ መስፍን፡- የመጀመርያው መወሰድ የሚገባው ጥንቃቄ ቢኖር ቤተ ክርስቲያን ደቀ መዛሙርትን ማፍራት ላይ ትኩረት ሰጥታ መሥራት ይጠበቅባታል የሚለው ነው። እውነተኛ ደቀ መዛሙርት ያላት ቤተ ክርስቲያን ስንዴውን ከእንክርዳዱና ከገለባው መለየት የሚችሉ ጠንካራና ሥር የሰደዱ የክርስቶስ ተከታዮችን ማፍራት ትችላለች። ለዚህ ደግሞ ቁልፍ ሚና የሚጫወተው ጤናማ የሆነውን የነገረ መለኮትና መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆነውን ትምህርት በማስተማር ምእመናን ክርስቶስን መስለው እንዲያድጉ ማድረግ ቤተ ክርስቲያን የግድ ልትከተለው የሚገባ መርሕ ነው። ከዚህም የተነሣ ልዩ የሆነ የትምህርት ንፋስና ልዩ ልምምድ በተከሰተ ጊዜ ምእመናን ያለምንም መናወጥ ባሉበት ፀንተው እንዲቆሙ አቅምን ያገኛሉ። ሌላው ከውጭ የሚመጡ ሰዎችን አስተምህሮና ልምምድ አስቀድሞ በማጥናት ለምእመናን በቂ ግንዛቤ ማስጨበጥ፣ ቤተ ክርስቲያንን ከመጠበቅ አንጻር የሚጫወተው ሚና ታላቅ ስለሆነ የቤተ ክርስቲያን መሪዎችና አገልጋዮች ጠንካራ ሥራ ሊሠሩ ይገባል እላለሁ።
መጋቢ መስፍን፡- የኮልፌና የአካባቢው ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት በሥሩ ዐሥራ ሦስት ቤተ እምነቶችን የያዘ ኅብረት ነው። ከየቤተ እምነቱ የተወከልን አንዳንድ መሪዎች በሳምንት አንድ ቀን ጠዋት ጠዋት እየተገናኘን የመጸለይ፣ የመመካከር፣ ልምድ የመለዋወጥና አብሮ የመሥራትን መጽሐፍ ቅዱሳዊ አካሄድን ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት በማድረግ ላይ እንገኛለን። አንተ እንዳልከው የተለያዩ የስሕተት አስተምህሮዎችና ልምምዶች ብቅ በሚሉበት ጊዜ በኅብረቱ ውስጥ አባል በሆኑ የሥነ መለኮት አጥኚዎች ጥልቅ የሆነ ዐውደ ጥናት በርእሰ ጉዳዩ ላይ ከሥር መሠረቱ እንዲዘጋጅ ካደረግን በኋላ ምእመናን ተገቢውን ግንዛቤ እንዲጨብጡና ለስሕትት አስተምህሮ እንዳይጋለጡ መረጃዎችን በጋራ እንሰጣለን፤ እናስተምራለን።
በኅብረቱ ሥር ላሉ የተለያዩ አገልጋዮች ትምህርቶችን፣ ሥልጠናዎችን የምናዘጋጅ ሲሆን፣ በየዓመቱ ለሃያ አንድ ቀናት በጾምና በጸሎት ለምድራችንና ለአፍሪካ መንፈሳዊና ኢኮኖሚያዊ ጉብኝት ትኩረት ሰጥተን እንጸልያለን። ለአርባ ቀን በጾምና በጸሎት የአምላካችንን ፊት የፈለግንበት ጊዜ እንደነበረም አስታውሳለሁ። ኅብረቱ በዚህ ዓመት አንድ የጀማ ስብከተ ወንጌል ከአንድ መንፈሳዊ አገልግሎት ጋር በጋራ ያዘጋጀ ሲሆን፣ ብዙዎች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የተጨመሩበት፣ ከተለያዩ እስራትና ደዌ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነጻ የወጡበትና ምእመናን የተጽናኑበት ጊዜ ነበረን። በተሠራው ሥራ ሁሉ ክብር ለአምላካችን ለእግዚአብሔር ይሁን! በዚህ አጋጣሚ በኮልፌና አካባቢው ያሉ አገልጋዮችንና ምእመናን ለኅብረቱ ጥንካሬና ለእግዚአብሔር መንግሥት በትጋት እየሠሩ በመሆናቸው እግዚአብሔር ዘመናችሁን ይባርክ ማለት እፈልጋለሁ።
Share this article:
The historical Christian positions on social issues don’t match up with contemporary political alignments.
“ወርኀ ጽጌ ወስደት” የተሰኘው ይህ ጽሑፍ፣ በወንጌላውያኑ ዘንድ ብዙ ትኩረት ስለማይሰጠውና ጌታ ኢየሱስ በሕጻንነቱ ወራት ከእናቱ ማርያምና ከዮሴፍ ጋር ወደ ግብፅ የተሰደደበትን ታሪክ መነሻ በማድረግ፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስለ ሁነቱ ያለውን ትርክት ያስቃኛል።
ʻመሪዎች ለሁሉም ዐይነት ተቋማዊ ችግር ፍቱን መድኃኒቶች ናቸውን?ʼ በርግጥ በአመራር ላይ ጥናት ያደረጉ ጥቂት የማይባሉ ምሁራን መሪዎችን እንዲህ ባለ መልክ አያቀርቧቸውም። እጅግ የተደነቁቱ የአመራር ዘይቤዎችም ሳይቀሩ (ለምሳሌ፡- ሎሌያዊ አመራር – “Servant Leadership” እና ተሃድሷዊ አመራር – “Transformational Leadership”) ላለንበት ተቋማዊም ሆነ አገራዊ ችግር ብቸኛ መፍትሔ እንዳይደሉ እነዚሁ ምሁራን ይስማማሉ። ይህን አቋማቸውን “Leadership is not a panacea to all our problems” በማለት ነው የሚገልጡት – መሪነት ለችግሮቻችን ሁሉ ፍቱን መድኃኒት አይደለም እንደማለት ነው። ይህ ሲባል ግን የመሪዎች ሚና እንደዋዛ የሚታይ ጉዳይ እንዳልሆነ ሊታሰብበት ይገባል።
Hintset Christian Society is a faith-based society founded in June 7, 2013 by a group of Christians who are committed to the expansion and edification of the Evangelical Churches of Ethiopia. The Ge’ez word ‘Hintset’, which means ‘to edify’ or ‘to build’, is intended to describe this commitment.
“ከመልእክተ ሕንጸት” በስተቀር፣ በድረ ገጹ ላይ የሚቀርቡ ማናቸውም ዝግጅቶች የሕንጸት ክርስቲያናዊ ማኅበር አቋምን ላይወክሉ ይችላሉ።
With the exception of “Hintset’s Editorial”, any pubication presented on the Website may not necessarily represent the position of Hintset Christian Society.
Hintset Christian Society is a faith-based society founded in June 7, 2013 by a group of Christians who are committed to the expansion and edification of the Evangelical Churches of Ethiopia. The Ge’ez word ‘Hintset’, which means ‘to edify’ or ‘to build’, is intended to describe this commitment.
“ከመልእክተ ሕንጸት” በስተቀር፣ በድረ ገጹ ላይ የሚቀርቡ ማናቸውም ዝግጅቶች የሕንጸት ክርስቲያናዊ ማኅበር አቋምን ላይወክሉ ይችላሉ።
With the exception of “Hintset’s Editorial”, any pubication presented on the Website may not necessarily represent the position of Hintset Christian Society.
Hintset Christian Society
Hintset’s latest news and articles of the week to encourage, challenge, and inform you.
Add comment