[the_ad_group id=”107″]

ካውንስሉ ከኅብረቱና ከአራቱ ቤተ እምነቶች ጋር የነበረውን አለመግባባት መፈታቱ ተነገረ

July 10, 2023
Screen-Shot-2023-07-10-at-7.11.44-PM-1

በኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል እና በኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት፣ በኢትዮጵያ ሙሉ ወንጌል አማኞች ቤተ ክርስቲያን፣ መሠረተ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን፣ በኢትዮጵያ ሕይወት ብርሃን ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም በኢትዮጵያ ገነት ቤተ ክርስቲያን መካከል የነበረው አለመግባባት መፈታቱን ዛሬ በስካይ ላይት ሆቴል በተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ ተነገረ።

ከካውንስሉ ምሥረታ ጀምሮ የነበረው አለመግባባት በአብያተ ክርስቲያናቱና በኅብረቱ መካከል የነበረውን ግንኙነት አሻክሮ የቆየ ሲሆን፣ ይህን ተከትሎም ኅብረቱና አራቱ ቤተ እምነቶች ከካውንስሉ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት እንዲያቋርጡ አድርጓቸው እንደ ነበር ይታወሳል።

“የጋራ ጕዳያችንን በአንድ ድምፅ የሚያስተጋባ አደረጃጀት ማስፈኑ በመንፈሳዊም ሆነ በአገራዊ አገልግሎታችን ውጤታማና ተጽእኖ ፈጣሪ ለመሆን” ያስችላል በሚል ያቋቋሙት መሆኑን የሚገልጸው መግለጫው፣ ይሁን እንጂ “ከካውንስሉ መቋቋም በፊት በተለያዩ አደረጃጀቶች ውስጥ የነበርን ቤተ እምነቶችና ኅብረቶች በመሆናችን በቀላሉ ወደ አንድ አሠራር ማምጣትና መግባባት ሳይቻለን ቆይቷል። በተለይም ካውንስሉ በአዋጅ ከተቋቋመበት ጊዜ ወዲህም ሆነ በፊት የነበሩ ተግዳሮቶችን ለመፍታት ሰፊ ጥናት የተደረገ ቢሆንም፣ ጠለቅ ያለ ውይይት እና ምክክር የሚፈልጉ ከውክልና፣ ከአደረጃጀት፣ ከደንብና አሠራር ጋር የተያያዙ ጕዳዮች ላይ ስምምነት መድረስ አልተቻለም። ይልቁንም ከአንደኛው መደበኛ ጠቅላላ ጕባዔ ጋር በተያያዘ ልዩነቱን አስፍቶት ቆይቷል።” ሲል የገጠመውን ችግር ያብራራል።

“አሁን ግን ለልዩነታችን ምክንያት በሆኑ ተግዳሮቶች ላይ በስፋት ከመከርን በኋላ፣ ካውንስሉ የተቋቋመበት ዐላማ መፈጸምና አገራዊ ተልእኮውንም መወጣት የሚያስችል ቁመና እንዲኖረው ለማድረግ፣ ወሳኝ አምስት ዋና ዋና የልዩነት ነጥቦችን በመለየትና ለእነርሱም አምስት የመፍትሔ ሐሳቦችን በማስቀመጥ እንደ እግዚአብሔር ቃል በመቀባበልና በመመካከር በጋራ ለመሥራት ተስማምተናል።” ይላል መግለጫው። 

“በመሆኑም በአገር ውስጥና በመላው ዓለም የምትገኙ የወንጌል አማኞች ስለተደረገው ዕርቅ ሁላችሁንም እንኳን ደስ አላችሁ” ያለው መግለጫ፣ “ወደ ፊት በምናደርገው የጋር እንቅስቃሴ ሁሉ በጸሎትና በምክር ከጎናችን እንድትሆኑ ጥሪያችንን እያስተላለፍን፣ በሁሉም ክልሎችና ዞኖች የምትገኙ አገልጋዮችና ምእመናን በሙሉ፣ ሥራዎችን በጋራ በመቀራረብና በመወያየት እንድታከናውኑና ስለተፈጠረው ዕርቅም በያላችሁበት እግዚአብሔርን እንድታመሰግኑ መልእክታችንን እናስተላልፋለን።” ብሏል። 

ከጋዜጣዊ መግለጫው በኋላ ንግግር ያደረጉት የካውንስሉ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጣሰው ገብሬ እና የኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ፕሬዚዳንት መጋቢ ጻድቁ አብዶ፣ በተደረሰው ስምምነት መደሰታቸውን ገልጸው፣ ስምምነቱ የማይቀለበስበት ደረጃ ላይ ደርሷል ሲሉ ተደምጠዋል። 

ዶ/ር ጣሰው ለልዩነት ምክንያት የሆኑትና በውይይት ስምምነት ላይ የተደረሰባቸው ነጥቦች ዐምስት መሆናቸው ተነግረዋል። እነዚህም፣ አንደኛ፤ በከፍተኛ አመራርና ወሳኝ ቦታዎች ላይ ኅብረቱና አራቱ ቤተ እምነቶች በቂ ውክልና የሌላቸው መሆኑ፣ ሁለተኛ፤ በጽሕፈት ቤት ቍልፍ ቦታዎች ላይ በቂ ውክልና የሌለ መሆኑ፣ ሦስተኛ፤ አግባብ ያልሆነ የኮታ ድልድል መሰጠቱ፣ አራተኛ፤ የቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች አደረጃጀትና ምዝገባን የሚመለከት የአሠራር ክፍተት መኖሩ፣ ዐምስተኛ፤ ስምምነት ላይ እስኪደረስ ድረስ በየትኛውም በኵል አሉታዊ መግለጫ አለመስጠት የተሰኙ ናቸው። 

“አራቱም ቤተ እምነቶች፣ እኛም እንደ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት እግዚአብሔር በዚህ ጕዳይ ፌቨር ሰጥቶናል ብለን ነው የምናስበው” ያሉት ደግሞ መጋቢ ጻድቁ ናቸው። ለዚህም ምክንያታቸውን ሲሰጡ፣ “ኅብረቱ ፈርሷል” በሚል እስከ ገጠር ድረስ የዘለቀ ወሬ ይነዛ የነበረ መሆኑ የፈጠረው ተጽዕኖ ቀላል እንዳልነበረ ሲናገሩ ተደምጠዋል። 

ወደ ስምምነት ያመጣው የዕርቅ ሂደት የጀመረው ግንቦት 9 ቀን፥ 2015 ዓ.ም. መሆኑን የገለጹት መጋቢ ጻድቁና ዶ/ር ጣሰው፣ ሂደቱ ከባድና ስሜት የተቀላቀለበት ውይይቶች የተካሄዱበት እንደ ነበረ አውስተዋል። ሆኖም ግን፣ በእግዚአብሔር ዕርዳታ፣ የነበረውን ልዩነት ለማጥበብ በነበረ ቍርጠኝነት ወደ ኋላ የማይመለስበት ደረጃ ላይ እንዲመጣ እግዚአብሔር ረድቶናል ሲሉ መስክረዋል። 

የካውንስሉ ጠቅላይ ጸሐፊ የሆኑት፣ ቄስ ደረጀ ጀምበሩ በበኵላቸው ስምምነት የተደረሰባቸው ነጥቦችን አስጠብቆ መሄድ አማራጭ የሌለው መሆኑን አጽንዖት በመስጠት የገለጹ ሲሆን፣ በቀጣይ ስምምነት እንዲደረስባቸው በሚገባቸው የካውንስሉ መተዳደሪያ ደንብ እና በውክልና ኮታ ቀመር ጕዳይ ላይ በጥናት የተደገፈ ዐሳብ አምጪ ሚና የተሰጣቸው፣ እያንዳንዳቸው ሰባት አባላት ያሉት የባለሙያዎች ኮሚሽን መዋቀሩን ይፋ አድርገዋል። ሁለቱም ኮሚሽኖች፣ በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሥራቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን፣ እስከዚያው ግን ዐበይት ውሳኔዎች በድምፅ ብልጫ ሳይሆን፣ በስምምነት እንዲወሰኑ መግባባት ላይ መደረሱ ተገልጿል።

ስምምነት በተደረሰበት የአመራር ድልድል መሠረት፣ ካውንስሉ ምክትል ፕሬዚዳንት እና ምክትል ጠቅላይ ጸሐፊ እንዲሾሙለት ተደርጓል። በዚህም መሠረት፣ ሐዋርያው ዮሐንስ ግርማ የካውንስሉ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው የተመረጡ ሲሆን፣ በምክትል ጠቅላይ ጸሐፊ ደረጃ የመንፈሳዊና ዓለም ዐቀፍ ዘርፍ ኀላፊ ሆነው የተሰየሙት፣ የቀድሞው የኢትዮጵያ ሙሉ ወንጌል አማኞች ፕሬዚዳንት የነበሩት መጋቢ ይልማ ዋቄ ናቸው። በጽሕፈት ቤት ደረጃ፣ የዓለም ዐቀፍ ግንኙነት መምሪያ ዳይሬክተር በመሆን ኀላፊነት የተሰጣቸው ደግሞ መጋቢ አሸብር ከተማ ናቸው። 

1 comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Latest News

ስለ ቤተ መጻሕፍት አደረጃጀት ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ሥልጠና ተሰጠ

“የቤተ መጻሕፍት አደረጃጀት” የተሰኘ የግማሽ ቀን ሥልጠና ለተለያዩ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናት ተወካዮች ተሰጠ። በሕንጸት የመጽሐፍ ክበብ አዘጋጅነት የተዘጋጀው ሥልጠና፣ ቅዳሜ ሚያዚያ 14 ቀን፥ 2015 ዓ.ም. በላቭ ኤንድ ኬር ማዕከል የተካሄደ ነበር። 

Read More »
SIGN UP FOR OUR NEWSLETTER.

Hintset’s latest news and articles of the week to encourage, challenge, and inform you.